ለማህበረሰባችን ያለን ቁርጠኝነት
በ MCAEL ተልዕኮአችን ጎልማሳ የእንግሊዝኛ ቋንቋ ተማሪዎችን እና እነሱን የሚያገለግሉ ፕሮግራሞችን በመደገፍ ማህበረሰባችንን የማጠናከር ሂደት ላይ የተመሰረተ ነው። ከፍተኛ ፍርሃት እና እርግጠኛ ያለመሆን ሁኔታ በሚፈጠሩበት ጊዜያቶች ላይ፣ ስለ እሴቶቻችን እና ለምናገለግላቸው ሰዎች ስላለን ቁርጠኝነት በግልጽ መናገር ለእኛ አስፈላጊ ነው።
በሚኒሶታ እና በሌሎች የሀገሪቱ ክፍሎች እየተከናወኑ ያሉትን የኢሚግሬሽን ህግ ማስከበር እርምጃዎችን የሚገልጹ እጅግ አሳሳቢ ሪፖርቶች፣ በመላው ሀገሪቱ በሚገኙ ስደተኛ እና ስደተኛ ባልሆኑ ማህበረሰቦች ውስጥ ከፍተኛ ስጋትን መፍጠራቸው ግልጽ የሆነ ነገር ነው። ስለሆነም፣ በሜሪላንድ በተለይም በሞንትጎመሪ ካውንቲ የሚኖሩ በርካታ ነዋሪዎች በአካባቢያችን የኢሚግሬሽን ህግ የማስከበር እንቅስቃሴዎች ሊጨምሩ ይችላሉ የሚል ስጋት ውስጥ መግባታቸው ተገቢ ነው። ይህ እርግጠኛ አለመሆን ሁኔታ የዕለት ተዕለት ኑሮን፣ የቤተሰብ መረጋጋትን፣ እንዲሁም ትምህርት እና የማህበረሰብ አገልግሎቶችን የመፈለግ ፍላጎትን የሚጎዳ ፍርሃት፣ ጭንቀት እና የመጋለጥ ስሜትን ይፈጥራል።
የዚህን ሁኔታ ተፅዕኖ በየቀኑ የቅንጅት አጋሮቻችን፣ በአስተማሪዎች፣ በተማሪዎች፣ በበጎ ፈቃደኞች፣ እንዲሁም በጓደኞቻችን እና በቤተሰቦቻችን ዘንድ እናያለን፣ ይሰማናልም። ስደተኞች በጅምላ እና ባልተገባ ሁኔታ እንደ ወንጀለኛ ወይም እንደ መንግስት ሸክም ተደርገው ሲቆጠሩ ጊዜ፣ ጉዳቱ ከቃላት ባለፈ የከፋ ይሆናል። ይህም መተማመንን ሊያናጋ፣ የማህበረሰቡን ደህንነት ሊሸረሽር እና የማህበረሰባችንን ማህበራዊ ትስስር ሊያዳክም ይችላል። ይህ እንዲሆን መፍቀድ የለብንም።
በታዋቂ የትምህርት ተቋማት፣ በመንግስት መሥሪያ ቤቶች እና በተለያዩ የፖሊሲ ድርጅቶች በሰፊ ጥናት የተደገፉ እና በደንብ የታወቁ እውነታዎችን በድጋሚ መግለጹ አስፈላጊ ነው። ሰነድ የሌላቸውን ጨምሮ ስደተኞች፣ በአሜሪካ ከተወለዱ ዜጎች ያነሰ ወንጀል እንደሚፈጽሙ፣ በቢሊዮን የሚቆጠር ዶላር ለአካባቢ፣ ለክልል እና ለፌዴራል ግብር እንደሚያበረክቱ፣ እንዲሁም በሥራ ኋይል እና አነስተኛ ንግዶችን በመፍጠር ረገድ ወሳኝ ሚና እንደሚጫወቱ በተደጋጋሚ ተረጋግጧል። እነዚህ ግኝቶች የግል አመለካከቶች አይደሉም፤ ለበርካታ አስርት ዓመታት በቆዩ አስተማማኝ ማስረጃዎች የተደገፉ ናቸው።
MCAEL በማህበረሰቦች እና በአካባቢ ተቋማት መካከል መተማመንን የሚያጎለብቱ፣ እንዲሁም ለህዝብ ደህንነት፣ ለጤና እና ለትምህርት ተደራሽነት አስፈላጊ የሆኑ ፖሊሲዎችን እና እሴቶችን ይደግፋል። እነዚህን መርሆች በሚገነዘብ እና እነሱን ለማስከበር በሚሰራ ካውንቲ ውስጥ በመኖራችን ደስተኞች ነን።
MCAEL ከተማሪዎቻችን፣ ከአጋሮቻችን፣ ከጎረቤቶቻችን፣ ከቤተሰቦቻችን እና ከማህበረሰባችን ጎን ይቆማል። ማንኛውም ሰው የኢሚግሬሽን ሁኔታው፣ የቋንቋ ችሎታው ወይም ብሔሩ ሳይለይ በፍትሃዊነት፣ በክብር፣ በርህራሄ እና በአክብሮት የመስተናገድ፣ እንዲሁም በቤቱ፣ በአካባቢው እና በዕለት ተዕለት ህይወቱ ደህንነቱ የተጠበቀ ሆኖ የመሰማት መብት እንዳለው እናረጋግጣለን። አዋቂ ተማሪዎችን እና እነሱን የሚያገለግሉ ፕሮግራሞችን ለመደገፍ፣ እንዲሁም በመላው የሞንትጎመሪ ካውንቲ ጽናትን፣ መተማመንን እና እድሎችን ለማጠናከር ከአጋሮቻችን ጋር በጋራ ለመስራት ያለንን ቁርጠኝነት እናረጋግጣለን።











